Latest News

ለአንድ ወር ከ15 ቀናት ሲካሄድ የነበረው ስፖርታዊ ውድድር ተጠናቀቀ

**********************************************************

[ግንቦት 24/2014ዓ/ም፤ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ-ባዳዩ] 

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ስፖርት አካዳሚ ከባሕር ዳር ከተማ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ጋር በመተባበር በታራሚዎች እና ፖሊስ አባላት መካከል ለአንድ ወር ከ15 ቀናት ሲካሄድ የነበረው ስፖርታዊ ውድድር ፍጻሜ በሰባታሚት ማረሚያ ቤት ግቢ በሚገኘው የስፖርት ሜዳ በተለያዩ ስፖርታዊ ውድድሮች እና ሽልማቶችን በማበርከት ተጠናቀቀ።

የባሕር ዳር ማረሚያ ቤት መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር አበርሃም ተስፋዬ የዚህ ስፖርታዊ ውድድር ዓላማ በታራሚዎች መካከል የእርስ በርስ ግንኙነት እንዲሁም ከፖሊስ አባላት ጋር ያለውን መልካም ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር፣ ሁሉም የህግ ታራሚዎች ከሌሎች መሰረታዊ የሙያ ስልጠናዎችና የቀለም ትምህርት ባለፈ የማረሚያ ቤት ቆይታቸውን በስፖርት እንቅስቃሴ በማሳለፍ በአካልም ሆነ በስነ-ልቦና እንዲታነጹ እንዲሁም በስፖርት እንዲዝናኑ ማድረግ የመጀመሪያው ዓላማ ሲሆን ሁለተኛው ጥሩ የስፖርት ችሎታ ያላቸውን ታራሚዎች እና አባላትን በመለየት ተቋሙን የሚወክል ጠንካራ ቡድን ማፍራት ነው። እነዚህን ዓላማዎች ከሞላ ጎደል አሳክተናል ማለት እንችላለን ብለዋል።

ኮማንደር አበርሃም አክለውም በቀጣይ ይህን መልካም ጅምር በርካታ ታራሚዎችን በስሜት እና በሞራል ያዝናና፣ ያስደሰተ መሆኑን ስለተረዳን ተቋሙ የራሱን አቅም በመጠቀም እና ስፖርቱን ሊደግፉ የሚችሉ መንግስታዊ እና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን በማፈላለግ፣ የስፖርት ግባቶችን በማሟላት ቀጣይነት እንዲኖረው በጋራ እንሰራለን ብለዋል። በተጨማሪም ከህግ ታራሚዎች የሚጠበቀው እንዳሳለፍነው የውድድር ወቅት መልካም ስነ-ምግባር መሆኑን ጠቁመው የተለያዩ ድርጅቶችም ስፖርቱን ከመደገፍ አኳያ ላደረጉት የገንዘብ፣ የጉልበት እና የሞራል አስተዋፅኦ ምስጋና በማቅረብ በቀጣይም ለሚከናወኑ የማረምና ማነፅ ተግባራት ሁሉ ቅን ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

የአብክመ ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን የህግ ታራሚዎች ማረምና ማነጽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር  አቶ ያዜ መኮንን በበኩላቸው “ይህ ውድድር ለስነ-ልቦና፣ ለአካል እና ለጤና አዎንታዊ አስተዋፅኦ ከማድረግ በተጨማሪ በታራሚዎች፤ በአባላትና በተቋማት እንዲሁም በግለሰብ ደረጃ ያለውን የእርስ በርስ ጤናማ የሆነ ግንኙነት የሚያጠናክር ሲሆን ለወደፊትም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡

ስፖርታዊ ውድድሩ የተካሄደው በታራሚዎች እና በፖሊስ አባላት መካከል ሲሆን የተካሄዱት የስፖርት አይነቶችም እግር ኳስ፣ ገመድ ጉተታ፣ ሩጫ እና መረብ ኳስ ሲሆኑ በእያንዳንዱ የስፖርት አይነት አሸናፊ ለሆኑ ቡድኖች የዋንጫ፣ የሜዳሊያ እና የማበረታቻ ሽልማት ተሰጥቷል፡፡ ለአስተባባሪዎችና ድጋፍ ላደረጉ የቤንማስ እና አዲስ አምባ ሆቴሎች እንዲሁም ግለሰቦች የምስጋና እና የምስክር ወረቀት በዝግጅቱ ላይ በተገኙ ተጋባዥ እንግዶች ተበርክቶላቸዋል።

የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የስፖርት አካዳሚ ምርምር እና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ዲን ዶ/ር ተከተል አብርሃም “በየዓመቱ የውስጥ ውድድር ከመካሄዱ በፊት ሁሉንም ታራሚዎች የአካል ብቃታቸውን እና የሥነ-ልቦና አቅማቸውን ለማጎልበት በተለያዩ የስፖርት አይነቶች በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ስፖርት አካዳሚ መምህራን አጫጭር ስልጠናዎችን በመስጠት ከማረሚያ ቤቶች ጋር በመተባበር ቀጣይነት እንዲኖረው ይደረጋል ብለዋል።

ዶ/ር ተከተል አያይዘውም ሌሎች መንግስታዊም ሆኑ መንግስታዊ ያልሆኑ ባለድርሻ አካላትና ደርጅቶች ለታራሚዎች የበኩላቸውን ድጋፍ እና እስተዋጽኦ በማድረግ የዜግነታቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ዘጋቢ፡- ባንቹ ታረቀኝ

 

The academy graduates 69 Officers In Charge Of an Engineering Watch Batch Number 19

Ethiopian Maritime Academy of Bahir Dar University graduated 69 Marine mechanical engineers who have been attending their six months long studies on June 1, 2022. This graduation is the 19th round since the establishment of the academy.

Speaking at the graduation ceremony, Mr. Birhanu Gedif, Vice president for administration affairs of Bahir Dar University told the graduates that they are not merely professional sailors in their work places, but are ambassadors of their academy, their university and their country. Congratulating the graduates the vice president emphasized the double responsibility the graduates shall shoulder.

Mr. Zelalem Teferi, Head of Human Resources and Administration Services at Bahir Dar University, Ethiopian Maritime Academy said that since the establishment of the academy, it has produced 1,870 sailors, including current graduates, serving in various shipping companies. The academy, the first in kind in Ethiopia and east Africa has been playing a significant role in building the image of the country, according to Mr. Zelalem.

At the graduation ceremony, the first graduate of the Ethiopian Maritime Academy chief Engineer Atakilt Kassa has been in attendance and he witnessed that the graduates of the academy are profoundly good and competitive in the international maritime industry.

Finally, certificates are awarded to top-scoring graduates.

5ኛው ሀገር አቀፍ የሎጂስቲክስና አቅርቦት ሰንሰለት አስተዳደር ጉባኤ ተካሄደ

*****************************************************************************

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ 5ኛው ሀገር አቀፍ የሎጂስቲክስና አቅርቦት ሰንሰለት አስተዳደር ጉባኤ "ዘላቂ የሎጂስቲክስና አቅርቦት ሰንሰለት አስተዳደር በኢትዮጵያ" በሚል ርዕስ  ግንቦት 23/2014 ዓ.ም በዩኒሰን ሆቴል በመስኩ የካበተ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች በተገኙበት ጉባኤውን አካሂዷል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር እሰይ ከበደ በጉባኤው ላይ ተገኝተው ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ባልተቀላጠፈ የሎጀስቲክስ ስርዓት ኢኮኖሚያዊ እድገትን ማረጋገጥ አይቻልም፤ የግብርና ዘርፉ ግብዓቶች፣  የፋብሪካ ማምረቻ ጥሬ እቃዎች እና የጤና ተቋማት የህክምና መገልገያ መሳሪያዎችን እና መድሃኒት ማምረትና ማከፋፈል፣ እንዲሁም አጠቃላይ የንግድ ስርዓቱ ያለ ሎጀስቲክስ እንደማይታሰብ ተናግረዋል፡፡

የሎጀስቲክስ አገልግሎት ለሀገራችን ማበርከት የነበረበት ድርሻ ከፍተኛ ቢሆንም መስኩ ተገቢውን ትኩረት ሳያገኝ እንደቆዬ በመስኩ ያስመረቅናቸው ተማሪዎች በስራ ገበታ የሚገጥማቸው ችግሮች ማሳያ ናቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ የዚህ አይነት አውደ-ጥናቶች በትምህርትና ምርምር ተቋማት እንዲሁም የጉዳዩ ባለቤት የሆኑ መስሪያ ቤቶች፤ የስራ ሀላፊዎችንና ሙያተኞችን የሚያገናኝ በመሆኑ በንድፈ ሀሳብና በተግባር መካከል ያሉትን መስተጋብሮች በመቀመር ቀጣይ አቅጣጫ ሊሆኑ የሚችሉ ሃሳቦችን ለማፍለቅ የሚረዱ ወሳኝ መድረኮች መሆናቸውን ዶ/ር እሰይ ተናግረዋል፡፡

የሎጀስቲከስ ዘርፉ ከወደብ፣ ከመንገድ፣ ከትራንስፖርት፣ ከሰለጠነ የሰው ሃይል፣ ከተቋማት ጋር ተቀናጅቶ የመስራት እና የውጭ ምንዛሬ ችግሮች እንዳሉበት ቢታወቅም ችግሮችን ደረጃ በደረጃ ለመቅረፍ የሚያስችል የመፍትሄ ሀሳቦች በአውደ ጥናቱ ላይ የቀረቡ የጥናት መረቀቶች አመላክተዋል፡፡ በአውደ ጥናቱ ላይ የኢትዮጵያ ትራንስፖርት ሚኒስቴር የማሪታይም ጉዳዮች ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ እውነቱ ታዬ እና የኤልያስ መልአክ ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ኤሊያስ መላክ የሎጀስቲክ ዘርፉ የተጋረጡበትን ችግሮችና የመፍተሄ ሀሳብን አስመልክቶ ቁልፍ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በአውደ ጥናቱ ላይ አቶ ስለሺ ካሴ “Logistics in Ethiopia: Practices, challenges and Future Prospects” የኢትዮጵያ የፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ እና ንግድ ሎጂስቲክስ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት የትራንስፖርት ባሕር ጉዳዮች ሚኒስቴር ዶ/ር መንግስት ሐይለማሪያም “Ethiopian logistics Industry: current Scenario and Future Outlook” የሚሉ ጥናታዊ ወረቀቶችን ጨምሮ አምስት የምርምር ስራዎች ቀርበው በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በመጨረሻም ለአውደ ጥናቱ መሳካት አስተዋጽዎ ላበረከቱ ኮሚቴዎችና ጥናታዊ ጽሁፍ ላቀረቡ ምሁራን  ተባባሪ ፕሮፌሰር እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ማቲዎስ እንሰርሙ እና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የምርምር እና ማህበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ተስፋዬ ሽፈራው በተገኙበት የምስክር ወረቀት ተበርክቶላቸዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ መሬት አስተዳደር ተቋም በከተማ መሬትና ፕላን ዘርፍ የስልጠናና ምዘና ፕሮግራም የማስጀመሪያ ስነ-ስርዓት አካሄደ

*******************************************************************

[ግንቦት 22/2014ዓ/ም፤ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ-ባዳዩ] የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የመሬት አስተዳደር ተቋም ከከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የከተሞች ገቢ ሪፎርም ፕሮጀክት ጽ/ቤት ጋር በመተባበር በከተማ መሬትና ፕላን ዘርፍ በተዘጋጁ የሙያ ደረጃዎች ማለትም ከደረጃ II እስከ V ለማሰልጠን እና የሙያ ብቃት ምዘና (COC) ለመመዘን የሚያበቃ የ45 ቀን ስልጠና የማስጀመሪያ ስነ-ስርዓት በ22/09/14 ዓ.ም በጥበብ ህንፃ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሄደ

የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዘዳንት ዶ/ር ተስፋዬ ሽፈረው እንደገለጹት ባሕር ዳር ኒቨርሲቲ በሁሉም የሙያ መስኮች በሚያስብል ደረጃ በከተማው በአራቱም አቅጣጫ የተለያዩ ግቢዎችን በማቋቋም ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ያለ አንጋፋ የትምህርት ተቋም መሆኑን አውስተዋል፡፡

ም/ፕሬዚዳንቱ አክለውም ይህን ስልጠና ለመስጠት ዝግጁ የሆነው ተቋምም የመሬት አስተዳደር ስርዓት ወጥነት እንዲኖረውና በዘመናዊ መልኩ ለማስተዳደር የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ገልፀው ሰልጣኞች በቆይታቸው ደስተኛ ሆነው ለላቀ ውጤት እንዲበቁ ከአደራ ጭምር አሳስበዋል፡፡

የኢ.ፊ.ዲ.ሪ ከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ ስልጠናውን ላመቻቸው ለባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ምስጋና አቅርበው በሰለጠኑ ዓለማት ያሉ ከተሞችን ተሞክሮ ስናይ የመሬት አስተዳደር ስርዓቱ በእውቀት የሚመራ ስለሆነ ስልጠናው ባለው እውቀታችን ላይ ክፍተቶችን ለመሙላት ያግዝ ዘንድ ትኩረት መሰጠት እንደሚገባው ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም ስልጠናው እኛው በእኛው በአገራችን ምሁራን መሰጠቱ አኩሪ ተግባር እንደሆነ አውስተዋል፡፡

ክብርት ሚኒስትሯ በማስከተል ስልጠናው የአሰልጣኞችም ሆነ የሰልጣኞች የጋራ ስለሆነ ሰልጣኞች በቁርጠኛነትና በነቃ ተሳትፎ ተከታትለው  በፅንሰ ሃሳብ ብቻ ሳይሆን በተግባር ላይ የዋለ የዳበረ ክህሎት እንዲሸምቱና ለጥሩ ውጤት እንዲበቁ መክረዋል፡፡

 

ከአማራ ክልል የከተማና መሰረተ-ልማት ቢሮ የመጡት ዶ/ር ኢብራሂም ሙሃመድ በበኩላቸው መሬት በአገራችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ይዘት ስላለው ይህን ሰፊ ጉዳይ ለማዘመንና ፍትሃዊ በሆነ መልኩ እንዲሰራ ብቁ ሙያተኞች ስለሚያስፈልጉት ስልጠናው የማንቂያ ደወል እንደሆነና በአይነቱ ላቅ ያለ መሆኑን ተናግረው ሰልጣኞች በአግባቡ እንዲሳተፉ አሳስበዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የመሬት አስተዳደር ተቋም ዳይሬክተር ዶ/ር በላቸው ይርሳው በበኩላቸው ስልጠናው ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ በአምስት ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚሰጥና ከነዚያ ውስጥ ተፎካካሪ ሆነው ስልጠናውን መስጠት መቻላቸው ዩኒቨርሲቲውን ብሎም ተቋሙን አንድ ደረጃ ከፍ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ስልጠናው ከግንቦት 21 አስከ ሰኔ 07/2014 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ መሆኑን ገልፀው ሰልጣኞች በቆይታቸው የተቋሙን ህግና ደንብ ማክበር እንዳለባቸው በአደራ መልኩ አሳስበው ቆይታቸው የተሳካ እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን ገልፀዋል፡፡

የስልጠናው የአሰጣጥ ስርዓት በተቋሙ መምህር የተገለፀ ሲሆን ሰልጣኞች ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍል የተውጣቱ ሲሆኑ በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ ክብርት ሚስትሯን ጨምሮ አብረው ለመጡ ልኡኮች ከዩኒቨርሲቲው ስጦታ ተበርክቶላቸዋል ፡፡

ሁለተኛዉ የአፍሪካ ግራጆይት ተማሪዎች አውደ-ጥናት በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በርካታ ጥናታዊ ፅሁፎችን በማቅረብ ተካሄደ፡፡

ሁለተኛዉ የአፍሪካ ግራጆይት ተማሪዎች አውደ-ጥናት በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጥበብ አዳራሽ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዝነኛ የሆኑ ፕሮፌሰሮች፣ የዩኒቨርሲቲዉ አመራሮች፣ ጥናት አቅራቢ ምሁራንና ጥሪ የተደረገላቸዉ እንግዶች በተገኙበት ከግንቦት 19−20/2014 ዓ.ም ተካሂዷል፡፡

በአውደ-ጥናቱ ተገኝተዉ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዘዳንት ዶ/ር እሰይ ከበደ የምርምር ፅሁፎችን ማቅረብ የዩኒቨርሲቲዉ ምሁራን ባህል እየሆነ መምጣቱን አዉስተዉ ለተመራቂ ተማሪዎች የሚመደበዉ የመመረቂያ በጀት ግን አነስተኛ በመሆኑ ችግሩ እንዲስተካከል ከባለድርሻ አካላት ጋር እየመከሩበት እንደሆነ ገልፀዋል፡፡

የእለቱ የክብር እንግዳ የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ከንቲባና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የቦርድ አባል ዶ/ር ድረስ ሳህሉ ለነዋሪዎቿ ምቹ፣ ዉብና ማራኪ በሆነችዉ ከተማ የሚገኘዉ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በ2030 እ.ኤ.አ ከአፍሪካ ቀዳሚዉ የምርምር ዩኒቨርሲቲ ለመሆን ጠንክሮ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡አያይዘዉም ዩኒቨርሲቲዉ የከተማዋን ሁለንተናዊ እድገት በማፋጠን ረገድ ከፍተኛ ስራ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጱያ ሳይንስ አካዳሚ ኢክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ተከተል ዮሐንስ በአውደ-ጥናቱ ተገኝተዉ አነቃቂ ንግግር አቅርበዋል፡፡በንግግራቸዉም የኢትዮጱያ ሳይንስ አካዳሚ የዓለም ሳይንስ አካዳሚ አባል መሆኑን በመጥቀስ አካዳሚዉ ጥናቶችን ማስጠናት ዋና አላማዉ እንደሆነና የተገኙ የጥናት ዉጤቶችንም ለመንግስትና ለፖሊሲ አዉጭዎች እንዲደርሱ ያደርጋል ብለዋል፡፡ፕሮፌሰር ተከተል አክለዉም ሳይንስ አካዳሚዉ አስራ አምስቱን አፕላይድ ዩኒቨርሲቲዎች እያገዘ መሆኑን በመጥቀስ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲም ልዩ ልዩ ጆርናሎችን በማሳተም እዉቅና ካገኑ ዩኒቨርሲቲዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በአሜሪካና በአዉሮፓ በሚገኙ ታላላቅ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሩትና በተለያዩ ሀገራት ከፍተኛ ተመራማሪዎችን ማስተማር የቻሉት ፕሮፌሰር ማሞ ሙጨ ለመድረኩ ተሳታፊዎች ንግግር አድርገዋል፡፡በንግግራቸዉም የእዉቀት፣ የሰብአዊነትና የነፃነት መሰረት የሆነዉ ሀገር በቀል እዉቀት የተገኘዉ ከኢትዮጱያ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ፕሮፌሰሩ አክለዉም የአፍሪካ የትምህርት ስርዓት  የቅኝ ገዥዎች የትምህርት ስርዓት እንደሆነ በመግለፅ ልክ እንደ ቻይና የራሳችንን የትምህርት ስታንዳርድ ማዘጋጀት አለብን ብለዋል፡፡በሀገር በቀል እዉቀት ዙሪያ ትኩረት ሰጥተዉ የተናገሩት ፕሮፌሰር ማሞ ከኢትዮጱያ የተፈጠረዉ ፊደልና የዘመን አቆጣጠር ለአለም ሊበቃ እንደሚችል የሌሎች ሀገራት ምሁራንም ይረዱታል ብለዋል፡፡ 

ለሁለት ቀናት የዘለቀዉ አውደ-ጥናት በማጠቃለያዉ በተሳታፊዎች አስተያየቶችና ጥያቄዎች ቀርበዉ ከመድረኩ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ተሳታፊዎችም በቆይታቸዉ ብዙ ቁም ነገር የጨበጡ በመሆኑ ደስተኞች መሆናቸዉን ተናግረዋል፡፡

በአውደ-ጥናቱ የማጠቃለያ ሃሳብ የሰጡት የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የድህረ ምረቃ ት/ቤት ኤክስኪዩቲቭ ዲን ዶ/ር ሙሉጌታ አድማሱ እንደገለፁት በመድረኩ ለመሳተፍ 155 የጥናት ወረቀቶች ቀርበዉ የተመረጡ 90 የምርምር ስራዎች በመድረኩ ማቅረብ ችለናል ብለዋል፡፡ዶ/ር ሙሉጌታ አክለዉም አውደ-ጥናት በሀገሪቱ የመጀመሪያዉና በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ለ2ኛ ጊዜ የተካሄደ የድህረ ምረቃ ተማሪዎች ብቻ የሚሳተፉበትና የምርምር ስራቸዉን የሚያቀርቡበት ነዉ ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ከ90 ጥናታዊ ፅሁፎች የተመረጡ የ5 ወንዶችና የ2 ሴቶች በድምሩ 7 ተመራማሪዎች ልዩ የማበረታቻ የምስክር ወረቀት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡

 

በሸጋዉ መስፍን

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

የትምህርትና ሥነ-ባህርይ ሳይንስ ኮሌጅ 39ኛውን አለማቀፍ ‘የግንቦት ሴሚናር’ አካሄደ

***********************************************************************

ባዳዩ ፣ግንቦት 20/2014 ዓ.ም

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የትምህርትና ሥነ-ባህርይ ሳይንስ ኮሌጅ የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዩበልዩ ክብረ በዓል እና 39ኛውን ዓመታዊ አለማቀፍ ’ግንቦት ሴሚናር’ በተለያዩ ትምህርታዊ ዝግጅቶች በዩኒቨርሲቲው የመሰብሰቢያ አዳራሽ ግንቦት 27 እና 28/2014 ዓ.ም አካሂዷል ፡፡

 

በአውደጥናቱ ላይ ዶ/ር መስከረም ሌቺሳ “The challenge of creating a globalization–classical Ethiopia through Education: The Nexus among National, International Commerce and Humanistic Focuses”   ፕሮፌሰር ያለው እንዳወቀ “Educational Inclusion: Political Rhetoric or Practical Concern? Analyzing the practices of inclusiveness in Ethiopian education” ፕሮፌሰር አለማየሁ ቢሻው “Ethiopian Higher Education Curriculum Reform” በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ረዳት ፕሮፌሰር አቶ አዳነ ተሰራ “May Annual International Educational Conference Development, Challenges and Prospects.” በሚል ርዕስ ከቀረቡት ጥናታዊ ፁሁፎች በተጨማሪ በአጠቃላይ 10 የምርምር ፅሁፎች ቀርበው በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

 

 

የዘንድሮውን የ39 ኛውን አለማቀፍ አውደጥናት ካለፉት ጊዚያት ለየት የሚያደርገው ኮሌጁ የ50ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ደርበን ያከበርንበት ቀን በመሆኑ የተለዬ ስሜት እንደፈጠረባቸው የትምህርትና ስነ-ባሕርይ ሳይንስ ኮሌጅ ዲን የሆኑት ዶ/ር አስናቀው ታገለ ገልፀው በአውደጥናቱ ላይ ጥናታዊ የምርምር ፁሁፍ ላቀረቡ ምሁራን የተሳትፎ የምስክር ወረቀት ሰጥተዋል፡፡

 

በአውደጥናቱ ላይ ጠንካራ የምርምር ስራዎች የቀረቡበት  ቀጣይነት ያለው የትምህርት ልማት አላማን ከማሳካት አንፃር መሰራት ያለባቸው ስራዎች የሚያመላክት አውደ ጥናት እንደነበር የአውደ ጥናቱ ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡

በአውደጥላቱ ላይ  የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ ኃላፊዎች፣ጥናትና ምርምር አቅራቢዎች፣ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ መምህራንና ተማሪዎች ታድመውበታል፡፡

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

+2

 

 

የትምህርት እና ስነ-ባሕሪ ኮሌጅ የተመሰረተበትን የወርቅ ኢዩቤልዩ በዓል አከበረ
ባዳዩ ፣ግንቦት 19/2014 ዓ.ም

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የትምህርትና ስነ-ባሕሪ ኮሌጅ የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ  በዓልን በጡሮታ የተገለሉ  የኮሌጁ ሰራተኞች፣ መምህራን እና ተማሪዎች እንዲሁም የቀድሞ ሙሩቃን ፣  የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በክልሉ ማርሽ ባንድ ታጅቦ ግንቦት 19/2014 ዓ.ም በዋናው ግቢ ስፖርት አካዳሚ ስታዲየም በደመቀ ሁኔታ አክብሯል፡፡

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የትምህርትና ስነ-ባሕርይ ሳይነስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር አስናቀው ታገለ በክብረ በዓሉ ላይ እንዳሉት  የቀድሞው የባሕር ዳር መምህራን ኮሌጅ (ፔዳ ጎጂ) ያሁኑ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የትምህርትና ስነ-ባሕርይ ሳይንስ ኮሌጅ በ1965 ዓ.ም በኢትዮጵያ መንግስት፣  በዩኒስኮ እና በUNDP ትብብር መመስረቱን ተናግረዋል፡፡ አክለውም በዛሬው እለት የ50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዩቤልዩ ክብረ በዓልን ስናከብር ውጤታማና ምስጉን መምህራንን እና የትምህርት አመራር ባለሙያዎችን ያፈራ ፤ የሌሎች የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ኮሌጆች፣ ፋኩሊቲዎች እና ትምህርት ቤቶች እናት፤  ዩኒቨርሲቲውን በመመስረቱ ረገድ ዋና እና የጀርባ አጥንት፤ ድንቁርናን ያለማቋረጥ ለተከታታይ 50 ዓመታት የተዋጋና በኢትዮጵያ የእውቀት ብርሐንን የፈነጠቀ ፤በሀገሪቱ የውጤታማና ስመጥር ተቋማት ተምሳሌትና የትምህርት አመራርና የልህቀት ማዕከል አንዱ እና ለባሕር ዳር ከተማ መኩሪያና መታወቂያ የሆነውን ተቋም መዘከር መሆኑን ጠቁመው በዓሉን ለማክበር የተሰበሰቡትን የአንጋፋው የቀድሞው የባሕር ዳር መምህራን ኮሌጅ ቤተሰቦች እንኳን ለ50ኛው የወርቅ ኢዩቤልዩ  በዓል አደረሳችሁ ብለዋል፡፡

የኮሌጁን የ50ኛ የወርቅ ኢዩቤልዩ  የምስረታ በዓልን በይፋ ያስጀመሩት  የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኢንፎርሜሽን ስትራቴጅክ ኮሙኒኬሽን ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዘውዱ እምሩ  እንዳሉት ኮሌጁ አሁን ላይ በሀገራችን ካሉ ጥቂት የትምህረት የልህቀት ማዕከላት አንዱ ከመሆኑም በላይ በአውሮፓውያን አቆጣጠር በ2019 ዓ.ም በኬምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ይፋ በተደረገው ሪፖርት በትምህርት የምርምር ስራዎች ከሰሃራ በታች ካሉ 20 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ ሆኖ መመዝገቡን  አስታውሰው አክለውም እንደ ኮሌጂም ሆነ እንደ ዩኒቨርሲቲ  ባለፉት 50 ዓመታት በተመዘገቡት ወጤቶች ረክቶ  የሚቆም ሳይሆን ሀገራችን ኢትዮጵያ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ እየደረሰባት ያለውን መዛነፎች ለመፍታት ምክኒያታዊ ትውልድ ለመፍጠር ኮሌጁ አብዝቶ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ እንደ ዩኒቨርሲቲ 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ከመጭው ሰኔ ወር ጀምሮ ለአንድ ሙሉ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች ለማክበር ሰፊ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው የትምህርትና ስነ-ባህርይ ሳይንስ ኮለጅ 50ኛ ዓመት አከባበርም የዚሁ የዩኒቨርሲቲው 60ኛ ዓመት በዓል አከባበር አንዱ አካል ሆኖ እንደሚወሰድ አብራርተዋል፡፡

በከሰዓቱ መርሃ-ግብር 39ኛው አለምአቀፍ ትምህርታዊ አውደጥናት በዋናው ግቢ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አራት ጥናታዊ ወረቀቶች የቀረቡ ሲሆን አውደጥናቱ ነገም ቀጥሎ እንደሚውል ታውቋል፡፡ በበዓሉ አከባበር ላይ የኮሌጁ የቀድሞ መምህራን የአስተዳደር ሰራተኞች የኮሌጁን የ50 ዓመት ጉዞን አስመልክቶ ለበዓሉ ተሳታፊዎች ንግግር አድርገዋል ፡፡ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ባህል ማዕከል፣ የአማራ ፖሊስ ማርሽ ባንድ እና  ሰርከሰ ቡድን ዝግጅቱን አድምቅውት ውለዋል፡፡

 

 

 

ለዩኒቨርሲቲው መምህራን በፈተና ዝግጅት ዙሪያ ስልጠና ተሰጠ

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፈተና ማዕከል በፈተና ዝግጅት ዙሪያ "Testing Development" በተሰኘ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ለዩኒቨርሲቲው መምህራን ከ17-18/09/14 ለሁለት ተከታታይ ቀናት ስልጠና ሰጠ::

የማዕከሉ ዳይሬክተር ዶ/ር ተመስገን መላኩ የስልጠናው ዋና ዓላማ መምህራኑ ለተማሪዎች ፈተና በሚያዘጋጁበት ወቅት መርህ የተከተለ የፈተና ዝግጅት እንዲያካሂዱ በማድረግ የተማሪዎችን ክህሎት ለማዳበርና ብቃታቸውን ከፍ ለማድረግ ታልሞ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ዶ/ር ተመስገን በማስከተል ስልጠናውን ለመስጠት መነሻ ሀሳብ የሆነው የሙያው ባለቤቶች በተዘጋጁት ፈተናዎች ዙሪያ ጥናት አካሂደው የፈተና መርህ ያልተከተሉ በርካታ ግድፈቶች በመገኘታቸው ሲሆን ይህን ክፍተት ለመሙላት ስልጠናው ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልፀዋል፡፡

በተጨማሪም ስልጠናው ከመማር ማስተማሩ ጎንለጎን የትምህርት ጥራትን ለማጎልበት ያለው ጠቀሜታ የላቀመ ሆኑንና በተለይም ከመምህርነት ሙያ ውጭ ላሉ መምህራን ስልጠናው አስፈላጊ ስለሆነ በመጀመሪያው ዙር ከተለያዩ ግቢዎች የተውጣጡ180 መምህራን ለማሰልጠን ታቅዶ የህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ 30 መምህራን በሁለቱ ቀናት የሰለጠኑ ሲሆን በየግቢው ያሉትን በቅደም ተከተል ለማሰልጠን የታቀደ መሆኑን ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል፡፡

ዶ/ር ተመስገን በማጠቃለያ ሃሳባቸው ስልጠናው ለወደፊት ቀጣይነት እንዳለውና ለሁሉም መምህራን ተደራሽ እንደሚሆን ተናግረው ዩኒቨርሲቲው ማንኛውም ሙያተኛ ወደ ስራ ከመሰማራቱ በፊት ስልጠና እንዲያገኝ ቢያደርግ ውጤታማ ስራ ማስመዝገብ እንደሚቻል አሳስበዋል፡፡

በሙሉጎጃም አንዱዓለም

"ጥበብ ለሁለንተናዊ የህብረተሰብ ለውጥ" በሚል መሪ ቃል አውደ ጥናት ተካሄደ

በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በሂዩማኒቲስ ፋኩልቲ ስር ያለው የሲኒማና ቴአትር ጥበባት ት/ክፍል "ጥበብ ለሁለንተናዊ የህብረተሰብ ለውጥ" በሚል መሪ ቃል የሲኒማ ቴአትር ጥበባት አሁናዊ ቁመና፣ተግዳሮቶችና መፃኢ እድል ላይ የሚመክር የግማሽ ቀን አውደ ጥናት በዩኒቨርሲቲው የቀድሞ ሴኔት አዳራሽ ግንቦት18/2014 ዓ.ም አካሄደ፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኢንፎርሜሽንና ስትራቴጂክ ኮሙኒኬሽን ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዘውዱ እምሩ ጥሪውን አክብረው ለመጡ እንግዶችና ለመላው ታዳሚዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክታቸውንና ፕሮግራሙን ላዘጋጀው አካል ምስጋና አቅርበው ት/ክፍሉ ከተቋቋመ አጭር ጊዜ ቢሆንም መድረኩን ማዘጋጀት መቻሉ ሊያስመሰግነው እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

ዶ/ር ዘውዱ በማስከተል ጥበብ እያዝናና ቁምነገርን የሚያስጨብጥ ስለሆነ አገራችን ኢትዮጲያ ካጋጠማት ችግር እንድትወጣ በኪነጥበብ ሰፊ ስራ መሰራት እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ አክለውም አውደ ጥናቱ ለወደፊት የትኩረት አቅጣጫዎች የሚለዩበትና ተተኪው ትውልድ አገርን የሚታደግ ይሆን ዘንድ ሰፊ ስራ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ም/ፕሬዚዳንቱ ጥበብ ከፖለቲካ ተለይቶ የሀገርን ህልውና መታደግ እንደሚችል አውስተው ለወደፊት የጥበብ ሰዎች ትውልድን የማዳን ስራ ስለሚጠበቅባቸው ውይይቱ መሬት የነካ ውጤት እንዲያመጣ መልካም ምኞታቸው እንደሆነ ገልፀው አውደ ጥናቱን በይፋ ከፍተዋል፡፡

በእንግዶችና በትምህርት ክፍሉ መምህራን ጥናታዊ ፅሁፍ የቀረበ ሲሆን ጥበብ ምን መምሰል እንዳለበትና ከምራባዊው ዓለም ተፅኖ ወጥቶ ኢትዮጲያዊ ይዘቱን ይይዝ ዘንድ በእንግዶች በቀረበው ገለፃ ለመረዳት ተችሏል፡፡

በመርሃ ግብሩ ላይ አቶ አያልነህ ሙላቱ፣ፕሮፊሰር አዱኛ ወርቁ፣የፊልም አዘጋጅና ፕሮዲውሰር አቶ ሄኖክ አየለን ጨምሮ ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ በርካታ የጥበብ ሰዎች፣ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ የትምህርት ክፍሉ መምህራንና ተማሪዎች የታደሙ ሲሆን በቀረቡት የመነሻ ሃሳቦች ላይ ሰፊ ውይይት ተካሂዶ ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

አቶ አያልነህ ጥበብን ለማዳበር የትምህርት ስርዓቱ መስተካከል እንዳለበትና ከታች ክፍል ጀምሮ ትውልዱ ትምህርቱን እንዲያገኝ አሳስበዋል፡፡

የፋኩልቲው ዲን ዶ/ር ሰፋ መካ በማጠቃለያ መልዕክታቸው ት/ክፍሉ በቅርቡ ተመስሮቶ ይህን መድረክ ማዘጋጀት መቻሉ ይበል የሚያስብል ተግባር መሆኑን አውስተው ለወደፊት በርካታ አኩሪ ተግባራትን ለማከናወን ዩኒቨርሲቲው ድጋፍና ክትትል እንዲያደርግ አሳስበዋል፡፡

በሙሉጎጃም አንዱዓለም

 

የሃምሳኛ አመት የወርቅ ኢዮቤልዩ በዓል አከባበርን አስመልቶ መግለጫ ተሠጠ

*******************************************************************************

የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ የትምህርትና ስነ-ባሕሪ ኮሌጅ የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ  በዓል አከባበርን አስመልክቶ በሰጠው መግለጫ በዓሉን በተለያዩ ዝግጅቶች እና ትምህርታዊ ሴሚናሮች ከግንቦት 19-20/2014 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚከበር እና  የበዓሉ አከባበርም እስከ ታህሳስ 15/2015 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ ትምህርታዊ ዝግጅቶች እንደሚከበር የኮሌጁ ዲን ዶ/ር አስናቀው ታገለ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል፡፡

የቀድሞው የባሕር ዳር መምህራን ኮሌጅ በ1965 ዓ.ም በኢትዮጵያ መንግስት፣  በዩኒስኮ እና በUNDP ትብብር ተመስርቶ እስካሁን በርካታ ታላላቅ ሰዎችን ያፈራ እና እያፈራ ያለ አንጋፋ ኮሌጅ ነው፡፡ በነገው እለት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዮቤልዩ  በዓሉን በተለያዩ ዝግጅቶችና ትምህርታዊ ሴሚናሮች መከበር ይጀምራል፡፡ኮሌጁ በአሁኑ ሰዓት በሀገራችን ኢትዮጵያ ካሉ የትምህርትና የአመራር የልሕቀት ማዕከላት አንዱ መሆኑን የተናገሩት የኮሌጁ ዲን ወደፊትም ኮሌጁ በላቀ ጥራት ለሀገሪቱ የተማረ  የሰው ሀይል ለማፍራት በትጋት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የኮሌጁን የ50 ዓመት ጉዞን በተመለከተ እስካሁን የመጣበትን ሂደት በመፈተሽና በማጥናት ቀጣይ የኮሌጁን ጉዞ በተሻለ አደረጃጀት ለማስኬድ ታስቦ የሚከበር በዓል መሆኑ ተገልጿል፡፡ ዶ/ር አስናቀው ታገለ  ለመምህራን፣ የአስተዳደር ሰራተኞች፣ ተማሪዎች እና የቀድሞ ሙሩቃን እንኳን ለኮሌጁ የሃምሳኛ አመት የወርቅ ኢዮቤልዩ  በዓል አደረሳችሁ በማለት መልካም ምኞታቸውን ገልፀዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኢንፎርሜሽን ስትራቴጅክ ኮሙኒኬሽን ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዘውዱ እምሩ በበኩላቸው የቀድሞው የባሕር ዳር መምህራን ኮሌጅ ዛሬ ላይ የ50ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን ሲያከብር የትምህርትና ስነ-ባህሪ ሳይንስ ኮሌጅ ተብሎ መጠራቱን ተናገረው፤  ዛሬ ላይ ሀገሪቱ ላለችበት ከፍተኛ የትምህርት ደረጃ በኢትዮጵያ የትምህርት ታሪክ ውስጥ ሰፊ ሚና ያላቸው የተለያዩ ሙሩቃን በስነ-ትምህርት ዙሪያ እና በሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች በጣም ሰፊ የሆነ ድረሻ የነበረውና ዛሬ ላይ ላሉት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና ለሁለተኛ ደረጃ መምህራንን በማፍራት በኩል ከፍተኛ ታሪክ የጀመረ እና ለሀገሪቱም ጉልህ አስተዋፆ የነበረው መሆኑን ገልፀዋል፡፡ እንደ ዶ/ር ዘውዱ ገለፃ ኮሌጁ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ሌሎች አካዳሚክ ክፍሎች ማለትም ሳይንስ ኮሌጅ፣ ሂውማኒቲስ ፋኩልቲ፣  የማህበራዊ ሳይነስ ፋኩልቲ እና ሌሎች አካደሚክ ክፍሎች የ50 ዓመት እድሜ ካለው የትምህርና ስነ-ባሕሪ ኮሌጅ የወጡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ታሪክ የሚጀምረው ቀደም ብሎ በተመሰረተው የባሕር ዳር ፖሊ ቴክኒክ ኢንስቲትዩት በመሆኑ  ዩኒቨርሲቲው የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት በዓሉን  2015 ዓ.ም  ሙሉውን ዓመት የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የ60ኛ ዓመቱን ለማክበር ሰፊ እንቅስቃሴ እና ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ዶ/ር ዘውዱ  በመግለጫቸው ተናግረዋል፡፡   

 

Pages