Latest News
የሥርዓተ-ፆታ እና ልማት ጥናቶች ትምህርት ክፍል እያካሄደ የነበረው አገር አቀፍ ጉባኤ ተጠናቀቀ
በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የማህበራዊ ሳይንስ ፋኩልቲ ስር የሚገኘው የሥርዓተ-ፆታ እና ልማት ጥናቶች ትምህርት ክፍል ከ "Friedrich Ebert Stiftung" ጋር በመተባበር "National conference on Contemporary Gender Issue" በሚል መሪ ቃል ሁለተኛውን አገር አቀፍ
ጉባኤ በባሕር ዳር ከተማ ከሚያዚያ 05-06/2014 ዓ.ም ለሁለት ተከታታይ ቀናት ተካሄዶ ተጠናቀቀ፡፡
የፋኩልቲው ዲን ዶ/ር ታዬ ደምሴ ለፕሮግራሙ መሳካት ጉልህ አስተዋፅኦ ላበረከቱት አካላት ምስጋናና ለታዳሚዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈው ጉባኤው አገር አቀፍ መሆኑ ለትምህርት ክፍሉ መጠናከር ያለው ፋይዳ የላቀ መሆኑንና ትምህርት ክፍሉም ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎችን በማሰልጠን ላይ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
መርሃ ግብሩን በንግግር የከፈቱት የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዘዳንት ዶ/ር እሰይ ከበደ በኢትዮጵያ ካሉት ዩኒቨርሲቲዎች የመጀመሪያዋ ሴት ፕሬዘዳንት ሆነው ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲን ያገለገሉት ክብርት አምባሳደር ዶ/ር የሽመብራት መርሻን ጨምሮ ለመላው ታዳሚዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ዶ/ር እሰይ አክለውም የጉባኤው መካሄድ ትምህርት ክፍሉን አንድ እርምጃ ከፍ እንደሚያደርገውና ለወደፊት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከሚቀርቡት ጥናቶች በመነሳት የወደፊት የትኩረት አቅጣጫ እንደሚለይ ተናግረዋል፡፡
የክብር እንግዳዋ ክብርት አምባሳደር ዶ/ር የሽመብራት መርሻ ይህን ጉባኤ ለመታደም ከሩቅም ከቅርብም ለመጡ ተሳታፊዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈው ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ቤታቸውም ቤተሰባቸውም መሆኑን አውስተዋል፡፡ በማስከተል ከአሁን በፊት ዩኒቨርሲቲውን በማገልገል ላይ እያሉ ት/ት ክፍሉን ለማቋቋም በርካታ ውጣ ውረዶችን እንዳሳለፉና በተለይ በአውሮፓ አገራት ያለውን የስርዓተ ፆታ የተራራቀ ልዩነት ተገንዝበው በአገራችንም የሴቶች ተሳትፎ ጎልቶ እንዲወጣ የዘወትር ህልማቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡
አምባሳደሯ በማስከተል በአገራችን "ስርዓተ-ፆታ" ሲባል የሴቶች ጉዳይ ብቻ አድርጉ የማየት የተሳሳተ አስተሳሰብ እንዳለና ዛሬ ላይ ያ አስተሳሰብ ተሰብሮ የሁሉም አጀንዳ መሆኑን የሚያመላክተው ይህ ደማቅ ጉባኤው መካሄዱ ይበል የሚያሰኝ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ጉባኤውም ት/ት ክፍሉ ከመዳህ ዘሎ በእግሩ መቆሙን ማሳያና የሴቶችን ተሳትፎ ከፍ ለማድረግ የማንቂያ ደወል እንደሆነ ዶ/ር የሽመብራት በደስታ ገልፀዋል፡፡
የእለቱን ቁልፍ መልዕክት ያስተላለፉት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሴቶች፣ ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ም/ኃላፊ ወ/ሮ ሰላም አለማየሁ በአገራችን ብሎም በክልላችን ሴቶች በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በፖለቲካው መስክ ያላቸው ተሳትፎና ውክልና አናሳ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ወ/ሮ ሰላም አክለውም ይህ የተሳትፎ ውስንነት ሴቶች የሚጠበቅባቸውን አስተዋፅኦ እንዳያበረክቱና ከድህነት አረንቋ እንዳይወጡ ቢያደርጋቸውም ጭቆናውን ተቋቁመው በሁሉም መስኮች ሴቶች እያስመዘገቡት ያሉት ቱርፋቶች በቀላሉ የማይታዩ መሆናቸውን አስገንዝበዋል፡፡
ምክትል ቢሮ ኃላፊዋ በማስከተል የስርዓተ-ፆታ እኩልነትን ለማረጋገጥ እየተሰሩ ያሉ አበረታች ተግባራት ቢኖሩም የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት የተለያዩ መሰናክሎች እንዳሉና ከእንቅፋቶችም መካከል በሴቶች ላይ ያለው የተዛባ አመለካከት፣ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች፣ጾታዊ ጥቃት፣የሴቶች የስራ ጫና፣ ተቋማዊ ተግዳሮቶች፣ወቅታዊ፣ሃገራዊና ክልላዊ ፈተናዎች በዋነኛነት ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በተጨማሪም የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሴቶች፣ ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ከባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በጋራ በመተባበር በርካታ አኩሪ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ገልፀው በአሁኑ ወቅት በክልላችን ብቸኛ የሆነውን የለውጥ መሪነት ለስርዓተ- ጾታ ዕኩልነት የስልጠና ማዕከል (Transformative Leadership For Gender Equality Training Center) በፈለገ ሕይወት ሪፈራል ሆስፒታል መዘጋጀቱን እንዲሁም በዩኒቨርሲቲው ሴኔት ፀድቆ የስልጠና ካሪኩለም ተዘጋጀቶለት በቅርቡ ስራ የሚጀምር መሆኑንና ዩኒቨርሲቲው ለሴቶች ተሳትፎ ፈር ቀዳጅነት በመሆን በተለያዩ ፕሮግራሞች የትምህርት አድል መፍጠሩን ም/ቢሮ ኃላፊዋ ገልፀዋል፡፡
ወ/ሮ ሰላም በመልዕክታቸው ማጠቃለያም የስርዓተ-ጾታ ጉዳይ የአንድ ጾታ ጉዳይ ብቻ አለመሆኑንና በአንድ ክንፍ መብረር አለመቻሉን ሁሉም ሊረዳው እንደሚገባ በአንክሮ ገልፀው እኩልነቱን ለማስረፅ ከቤተሰብ ጀምሮ ት/ት ቤቶችና የሐይማኖት ተቋማት፣ የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ እንዲሁም ምሁራን ሰፊ ሚና መጫወት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
የጽሁፍ አቅራቢዎች አገር በቀል ምሁራን በመሆናቸው ሴቶቸን የማብቃት ስራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ወደ አመራሩም ሲመጡ ወንበሩን ብቻ መስጠት ሳይሆን የውሳኔ ሃሳብ እንዲያቀርቡ ማድረግ ተገቢ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በሙሉጎጃም አንዱዓለም
ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ
ባዳዩ-BDU
ከዓባይ ጓዳ ጥበብ ሲቀዳ
Wisdom at the source of Blue Nile
Thank you for Inviting, liking, sharing & visiting BDU pages!
ለተጨማሪ መረጃዎች፡-
Telegram ፡- t.me/BDU_ISC_Official
Main Website :- www.bdu.edu.et
Facebook: - https://www.facebook.com/bduethiopia
YouTube ፡- www.youtube.com/c/BduEduEt
LinkedIn ፡- www.linkedin.com/school/bahir-dar-university
Twitter: - https://twitter.com/bdueduet
በመጪው ብሔራዊ ውይይት ተስፋዎች እና ፈተናዎች ላይ ውይይት ተደረገ
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ማህበራዊ ሳይንስ ፋኩልቲ ከFRIEDRICH EBERT STIFTUNG ጋር በመተባበር ‹‹መጪው ብሔራዊ ውይይት ተስፋዎች እና ፈተናዎች›› በሚል ጭብጥ የግማሽ ቀን አውደ-ጥናት በዋናው ግቢ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አካሄደ፡፡
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር እሰይ ከበደ በመክፈቻ ንግግራቸው ባለፉት አስርት ዓመታት እንደ ህዝብ በብዙ ችግሮች ያለፍን እንደሆነ በመገንዘብ ለነዚህ ችግሮች ምንጭ የሆኑትን በመለየት ምሁራኑ ችግሮችን እንድናልፋቸው ዘንድ በትኩረት መስራት እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ ብዝሃነታችን አዙሮ በመጠቀም በመካከላችን መከፋፈል፣ መጠላላት፣ መገዳደል እንዲኖር የሚሰሩ ኃይላት እንደመሮራቸው ችግሮች እንዳይከሰቱ በትጋት መስራት ይገባል ብለዋል ዶ/ር እሰይ ከበደ፡፡
በሴሚናሩ Ethiopians Identity Crisis: Way Forward For the National Dialogue በፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ ፣ The Politics and Practices of Adjudicative and Deliberative Institution in Ethiopia: Lessons from Recent History በዶ/ር ተካልኝ ወልደማሪያም፣ Do No Harm: Managing Expectation in National Dialogue በፕሮፌሰር ሹመት ሲሻኝ፣ The Conflict in Northern Ethiopia and Its Ramifications በዶ/ር ቴዎድሮስ ሃይለማሪያም የተሰኙ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ማህበራዊ ሳይንስ ፋኩልቲ ዲን ዶ/ር ታዬ ደምሴ በበኩላቸው የዚህ አይነት ውይይት ቀጣይነት ያለው መሆኑን ጠቁመው የጥናታዊ ፅሁፎች አቅራቢዎችን እና ለዝግጅቱ መሳካት አስተዋፆ ያደረጉ አካላትን አመስግነዋል፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ ክብርት አምባሳደር ዶ/ር የሽመብራት መርሻን ጨምሮ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፤ የትምህርት ክፍሉ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው ከተለያዩ ሴክተር መስሪያ ቤቶች የተውጣጡ ምሁራን እና ጥናት አቅራቢዎች ተሳትፈዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ወንዳለ ድረስ
የሰባታሚት ማረሚያ ቤት ስፖርታዊ ውድድሮችን ማካሄድ ጀመረ
*******************************************************
የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ስፖርት አካዳሚ ከባሕርዳር ከተማ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ጋር በመተባበር በማረሚያ ቤት ለሚገኙ የህግ ታራሚዎች ሰባታሚት በሚገኘው የማረሚያ ቤቱ ስፖርት ሜዳ ከሚያዚያ 7/2014 ዓ.ም ጀምሮ ስፖርታዊ ውድድር ማካሄድ ጀምሯል፡፡
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ስፖርት አካዳሚ የስፖርት ሳይንስ መምህር የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ዘመኑ ተሾመ ፕሮግራሙን ሲከፍቱ እንደገለጹት ውድድር ማካሄድ ያስፈለገበት ምክንያት ታራሚዎች በቆይታቸው ከብቸኝነትና ተስፋ ከመቁረጥ ስሜት እንዲወጡ ለማድረግና አካላዊ እና አዕምሯዊ ጤናቸው ተጠብቆ የፍረድ ጊዜያቸውን ጨርሰው ሲወጡ መልካም እና ብቁ ዜጋ እንዲሆኑ በማሰብ ነው ብለዋል፡፡
የአብክመ ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን የህግ ታራሚዎች ማረምና ማነጽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ያዜ መኮነን በበኩላቸው ውድድሩ ለስነ ልቦና፣ ለአካል እና ለጤና ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከማድረጉ በተጨማሪ በታራሚዎች እና በማረሚያ ቤቱ አባላት መካከል ጤናማ ግንኙነት እንዲኖር ያግዛል ብለዋል፡፡ ውድድሩ ለአንድ ወር ከ15 ቀን እንደሚቆይም ገልፀዋል፡፡
ስፖርታዊ ውድድሩ የተካሄደው በታራሚዎችና በጥበቃ ሰራተኞች (ወታደሮች) መካከል ሲሆን በውድድሩ ላይ የተካሄዱት የስፖርት አይነቶችም መረብ ኳስ፣ ገመድ ጉተታ እና እግር ኳስ ናቸው፡፡
በመጨረሻም የዚህ ፕሮግራም አዘጋጅ ከሆኑት መካከል የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ስፖርት አካዳሚ ስፖርት ሳይንስ መምህር አቶ ዳንኤል ጌትነት የፕሮግራሙን መጀመር ታራሚዎች በጉጉት ሲጠብቁት እንደነበር በመግለፅ ቀጣይነት እንዲኖረውም የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲም ሆነ ሌላው የማህበረሰብ ክፍል ለስፖርታዊ ውድድሩ አስፈላጊ የሆኑ የቁሳቁስ ድጋፎችን ቢያደርግልን የሚል መልክት አስተላልፈዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ባንቹ ታረቀኝ
ለማኔጂንግ ዳይሬክተሮችና የሰዉ ሀብት ልማት ዳይሬክተሮች አዲስ የሶፍዌር ስልጠና ተሰጠ
በከፍተኛ ትምህርት የመረጃ አያያዝ ስርዓት ላይ ትኩረቱን ያደረገ ስልጠና በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ለማኔጂንግ እና የሰዉ ሀብት ልማት ዳይሬክተሮች ፔዳ ግቢ በሚገኘዉ የአይሲቲ ስልጠና ማዕከል በአይሲቲ ዳይሬክቶሬትና በበጀትና ልማት ዳይሬክቶሬት ትብብር ተሰጥቷል፡፡
በስልጠናዉ ላይ የመግቢያ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲዉ በጀትና እቅድ ዳይሬክተር አቶ ሽመልስ በቀለ እንደገለፁት ስልጠናዉ ለአስተዳደር ዘርፉ ለሁለተኛ ጊዜ እየተሰጠ መሆኑን ገልፀዉ ከስልጠናዉ የሚገኙትን መሰረታዊ ጥቅሞች አብራርተዋል፡፡ አቶ ሽመልስ እንዳሉት መረጃዎችን በዚህ ሶፍትዌር ማስቀመጥ ለዉሳኔ ሰጭ አካላት ትክክለኛ መረጃዎችን ለመስጠት ያስችላል፤ እንዲሁም ለድጋፍ፣ ለቁጥጥርና ለሪፖርት ግብዓት ይሆናል ብለዋል፡፡
ስልጠናዉን በማስተባበርና በመስጠት ላይ የነበሩት የዩኒቨርሲቲዉ የአይሲቲ ዳይሬክተር አቶ ይበልጣል ማሩ በበኩላቸዉ ስልጠናዉ በሀገር አቀፍ ደረጃ በትምህርት ሚኒስቴርና ሌሎች አለም አቀፍ አጋር አካላት በተሰራዉ የዩኒቨርሲቲዎች የመረጃ አያያዝ ስርዓት ላይ የአጠቃቀም ስልጠና መስጠትና ወደ መረጃ ቋቱ የሚገቡ መረጃዎችን እንዲገነዘቡ ማስቻል ነዉ ብለዋል፡፡ አቶ ይበልጣል አክለዉም ስልጠናዉ ባለፉት ሰባት ቀናት ከሌሎች የዩኒቨርሲቲዉ ባለድርሻ አካላት ጋር ሲደረግ እንደነበር ገልፀዉ በቀጣይም ለሚመለከታቸዉ አካላት ይሰጣል ብለዋል፡፡
የስልጠናዉን አላማ አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጡት አቶ ይበልጣል ማሩ ሶፍትዌሩ አጠቃላይ መረጃዎችን በሲስተም በማስገባት በሚፈለጉበት ጊዜ ጥቅም ላይ ለማዋል ያስችላል ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፦ ሸጋዉ መስፍን
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በቴክኖሎጂ የቢዝነስ ሃሳብ ውድድር ዙሪያ ስልጠና እየሰጠ ነው
የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የተመሰረተበትን 60ኛ ዓመት በዓል በማስመልከት በቴክኖሎጂ የቢዝነስ ሃሳብ ውድድር (Techno-Business Idea Competition) ዙሪያ ስልጠና እየሰጠ ነው፡፡
የዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር ሰይፉ አድማሱ እንደገለፁት ዩኒቨርሲቲዉ 60ኛ ዓመቱን ከመጭዉ መስከረም እስከ ሰኔ 4/2015 ዓ.ም ድረስ በልዩ ልዩ ፕሮግራሞች እንደሚያከብርና የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የ60 ዓመት ጉዞዉን ሊያሳይ በሚችል መልኩ በግብርና፣ በህክምና እና በሌሎች ዘርፎች ላይ ያለዉን እድገት ለመደገፍ እያከናወነ ያለዉን ስራ ለማሳየት ያለመ ነዉ ብለዋል፡፡
በስልጠናዉ የኢንስቲትዩቱ ተማሪዎችና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች የተገኙ ሲሆን በስራ ፈጠራቸዉ በሀገር አቀፍ ደረጃ ተወዳድረዉ ከስራ ፈጠራና ክህሎት ሚኒስቴር ዕዉቅናና ሽልማት የተሰጣቸዉ ተማሪዎች ስራቸዉን ለተሳታፊዎች አቅርበዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲዉ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሜከር ስፔስ አስተባባሪ (BIT maker space coordinater) ወ/ሪት ቤዛወርቅ ጥላሁን እንደገለፁት ፕሮጀክቱ የዩኒቨርሲቲዉ 60ኛ ዓመት ሲከበር መቅረቡ ተቋሙን በሚገባ ከማስተዋወቅ ባለፈ ተማሪዎቹ ስራ ፈጣሪ እንዲሆኑ ያደርጋል ብለዋል፡፡ ወ/ሪት ቤዛወርቅ አክለዉም ፕሮጀክቱ በአራት ዋናዋና መስኮች ላይ እንደሚሰራ ገልፀዋል፡፡ የትኩረት መስኮቹም የህክምና ቴክኖሎጂ፣ የግብርና ቴክኖሎጂ፣ የምግብ ማቀነባበርና ተረፈ ምርቶችን መልሶ ጥቅም ላይ በማዋል ዙሪያ እንደሚሰራ ተገልጿል፡፡
ስልጠናዉ ለሚቀጥሉት አራት ቀናት በገለፃና በመስክ ምልከታ የሚቀጥል መሆኑ መርሀ ግብሩ ላይ ተገልጿል፡፡
ዘጋቢ፡- ሸጋዉ መስፍን
8ኛው አገር አቀፍ የቋንቋ፤ባህልና ስነ-ተግባቦት ዐውደ-ጥናት ተካሄደ
በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የሂዩማኒቲስ ፋኩልቲ አዘጋጅነት 8ኛው አገር አቀፍ የቋንቋ፤ባህልና ስነ-ተግባቦት ዐውደ-ጥናት በዋናው ግቢ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሄደ፡፡
በመርሃ ግብሩ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ ሂዩማኒቲስ ፋኩልቲ ዲን ዶ/ር ሰፋ መካ የጉባኤው መሰረታዊ አላማ ፋኩልቲው ስልጠና በሚሰጥባቸው የቋንቋ፣ የባህል፣ የስነ ፅሁፍ፣ የጋዜጠኝነት እና ስነ ተግባቦት ጥናት ዘርፎች እንዲቀርቡ በማድረግ ግኝቶቹ ህብረተሰቡ እንዲያውቃቸው እና እንዲጠቀምባቸው ምቹ ሁኔታ መፍጠር ሲሆን ቋንቋ፣ ባህል እና ማንነት መልካም አጋጣሚ ወይስ ስጋት በሚል አጠቃላይ ጭብጥ ላይ የተመሰረተ ነው ብለዋል፡፡
ዶ/ር ሰፋ አክለውም 8ኛው አገር አቀፍ ዐውደ ጥናት ከቀደሙት ጉባኤዎች በአላማ አንድ ቢሆንም አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ በተለይም በአገራችን ውስጥ ጎሳን መሰረት ያደረገ ግጭት ጋር በተያያዘ ጠቃሚና ደረጃቸውን የጠበቁ ጥናቶችንና የመፍትሄ ሀሳቦች የቀረቡበት መሆኑ ለየት እንደሚያደርገው ጠቁመዋል፡፡
አውደ ጥናቱ በአገር አቀፍ ደረጃ የተካሄደ ሲሆን ከዩኒቨርስቲው ኢንፎርሜሽንና ስትራቴጂክ ኮሚኒኬሽን ባሻገር ከሠላም ሚኒስቴር እና ሀገር በቀል ዩኒቨርስቲዎች በመጡ ምሁራንና ተመራማሪዎች የተለያዩ ፅሁፎችን በማቅረብ የተሳተፉበት ነው፡፡
በጉባኤው ባህል፣ ቋንቋ እና ማንነት እንዲሁም ወቅታዊ ፈተናዎች እና እድሎች ዙሪያ መሰረት ያደረጉ ስምንት የጥናት ፅሁፎች የቀረቡ ሲሆን በውይይቱም ተማሪዎች፣ መምህራንና ሰራተኞች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ወንዳለ ድረስ
የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የአሳ ሃብትን በዘመናዊ መንገድ ጥቅም ላይ ማዋል ይገባል
ሙሉ ዜናውን ለማንበብ ማስፈንጠሪያውን ይከተሉ፡ https://www.facebook.com/ethiopianewsagency/posts/3173469222895535
ባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ከሰላም ሚኒስቴር ጋር የምክክር መድረክ አካሄደ
**************************************************
የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት ዙሪያ በፕሬዘዳንት ጽ/ቤት መጋቢት 22/2014ዓ.ም የጋራ ውይይት አካሄደ፡፡
ውይይቱን የመሩት የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር ጉዳዮች ተቀዳሚ ዳይሬክተር አቶ ገደፋዉ ሽፈራዉ እና ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የመጡት አቶ ንጉሱ ታደሰ ናቸው፡፡
የዩኒቨርሲቲው የተማሪዎች ዲን ዶ/ር ምንይችል ግታው ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ከሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች በተለየ መልኩ የተማሪዎችን ሕብረትና የሰላም ፎረም በፓርላማ ደረጃ አዋቅሮ እየሰራ መሆኑን አውስተው አደረጃጀቱም ለሰላማዊ መማር ማስተማሩ ያለው ፋይዳ የጎላ በመሆኑ አሁን ላይ ባለው ተጨባጭ ሁኒታ ችግር የማይሰማበት ሞዴል የሰላም ዩኒቨርሲቲ መሆኑንን ተናግረዋል፡፡
ዲኑ በማስከተል ለሰላሙ በር ከፋች የሆኑት ሌሎችንም መልካም ተሞክሮዎች እንደ ባሕር ዳር እንደቤቴ (በበዓል ዕለት ከሌላ ቦታ የመጡትን ተማሪዎች በከተማው ውስጥ ባሉ በጎ ፈቃደኛ ቤተሰብ በዓሉን እንዲውሉ የሚደረግበት) ፕሮግራም፣ከተማሪዎች፣ከሰራተኞችና ከከተማው ማህበረሰብ ጋር በሰላሙ ዙሪያ ሰፊ ውይይት በማድረግና በመተማመን የሚሰራው ሰፊ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉ ሰላሙ እንዲሰፍን ማድረጋቸውን አስገንዝበዋል፡፡
አቶ ገደፋውም በበኩላቸው በዩኒቨርሲቲው ፍፁም የሆነ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀው ሰላም እንዲሰፍን ከሚያደርጉት ነገሮች መካከል በዩኒቨርሲቲው ውስጥ የተጠናከረ የበር ፍተሻ መኖሩ፣ ፌደራል ፖሊስ ተመድቦ እየሰራ መሆኑ፣ተማሪዎች በየግቢያቸው በሰላሙ ዙሪያ እየሰሩ በመሆኑ እና የየግቢዎች አረንጓዴ ልማት መስፋፋት የመሳሰሉት ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡
ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የመጡት እንግዶች አቶ ንጉሱ ታደሰ እና አቶ ደመቀ ቢያዝን ከዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የቀረበው ገለፃ ፍፁም ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እየተከናወነ መሆኑን ስለሚያመላክትና ለዚህ ሰላም መስፈን ለተደረገው ጥረት ላቅ ያለ ማስጋና አቅርበዋል፡፡
አቶ ንጉሱ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከአብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል ጋር መስራታቸውን ተናግረው በአመዛኙ ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ሰፊ ስራ እንደሚሰሩና አገራዊም ሆነ ብሄራዊ መግባባቶች አስፋላጊ እንደሆኑ በአንክሮ ተናግረዋል፡፡
አክለውም በግቢዎች ውስጥ የሚታዩትን ተግዳሮቶች ከዚያው ሳይወጡ በቶሎ የመፍታት ልምድ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበው የሰላም ፎረሙም በየጊዜው ጠንካራና ደካማ ጉኑን በመመርመር ማስተካከል የሚቻልበትን ሁኔታ ማመቻቸት ለሰላም መስፈኑ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
አቶ ደመቀም እንደገለፁት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች ብቻ ሳይሆን በሰላማዊ ቦታም በመገኘት ሰላሙ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚሰራ ተቋም መሆኑን ገልፀው በቅርቡ ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር ከ1ኛ ክፍል ጀምሮ የግብረ-ገብ ትምህርት እንዲሰጥ የስምምነት ሰነድ መፈራረማቸውን ተናግረዋል፡፡
ታዳሚዎች ጉዳዩ የሚመለከታቸው የዩኒቨርሲቴው የስራ ኃላፊዎችና የክልሉ የሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ኃላፊ ሲሆኑ ሁሉም ሰላማዊ የመማር ማስተማሩ ሰፊ ስራ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በመርሃ ግብሩ ላይ በዩኒቨርሲቲው የውስጥ ግንኙነት አቶ ግርማው አሸብር አማካኝነት ዩኒቨርሲቲውን የማስተዋወቅ ስራ ተከናውኗል፡፡
ዘጋቢ፡- ሙሉጉጃም አንዱዓም