ሰልጣኞች እንቦጭን በመንቀል ተሳተፉ

5ኛው ዙር የበጎነት ለአብሮነት ብሔራዊ አገልግሎት ሰልጣኞች እንቦጭን በመንቀል ተሳተፉ

(ሕዳር 22/2015ዓ/ም ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ)  የ5ኛው ዙር የበጎነት ለአብሮነት ብሔራዊ አገልግሎት ሰልጣኞች በባሕር ዳር ከተማ አፄ ምኒልክ ክፍለ ከተማ ሰባታሚት ቀበሌ የአባይ ወንዝ በሚያዋስናቸው አካባቢዎች የእንቦጭ አረምን በመንቀል በበጎ ፍቃድ አገልግሎት ስራዎች ላይ ተሳተፉ፡፡

ሰልጣኞችን ሲያስተባብሩ ያገኘናቸው ረዳት አሰልጣኝ ኢምራን አብዱሰመድ እንዳሉት በእንቦጭ ማረም ስራው ሁሉም የ5ኛው ዙር የበጎነት ለአብሮነት ብሔራዊ አገልግሎት ሰልጣኞች የተሳተፉ ሲሆን ካሁን በፊትም ከምግባቸው ቀንሰው ለጎዳና ተዳዳሪዎች ምግብን ማጋራታቸዉን ተናግረዋል፡፡

በአፄ ምኒልክ ክፍለ ከተማ ሰባታሚት ቀበሌ አስተዳደር የሰብል፣ አትክልትና ፍራፍሬ ባለሙያ አቶ ገበያው አስቻለው አባይ ወንዝ በሚያዋስናቸው ምዕራብና ምስራቅ አቅጣጫ ለመስኖ ስራ እንዲውል በተሰሩ ቦዮች ሁሉ በእንቦጭ አረም ተወረዉ የሚገኙ ሲሆን ይህን ለመከላከል እንደ ክልል በሚሰራው የተፈጥሮ ሀብት ስራ አርሶ አደሮችን እና የአካባቢውን ህብረተሰብ በማስተባበር እየሰራን እንገኛለን ብለዋል፡፡ ዛሬ ላይ በ5ኛው ዙር የበጎነት ለአብሮነት ብሔራዊ አገልግሎት ስልጠና የወስዱ ወጣቶች በቀበሌያችን ተገኝተው የእንቦጭን አረም ለማስወገድ ያደረጉት አስተዋፅዖ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡

በበጎ ፈቃድ የተሰማራችው ተማሪ ብርቱካን ወንዴ በበኩሏ ከአሁን በፊት ብዙ የበጎ ስራዎች ላይ መሳተፏን ገልፃ አሁን ላይ በብዙ ቦታዎች ተንሰራፍቶ የሚገኘውን እንቦጭ በመንቀል የዜግነት ግዴታዋን በመወጣቷ ደስተኛ መሆኗን ተናግራለች፡፡