ዶ/ር ሲሳይ መንግስቴ የኢፌዲሪ ህገ-መንግስት ክለሳ/ማሻሻል አስፈላጊነት በሚል ርዕስ በፔዳ ግቢ ኦዲተርየም አዳራሽ ህዝባዊ ጉባዔ አቅርበዋል፡፡ምሁሩ በንግግራቸዉ መንደርደሪያ በሀገራችን የተፃፈ ህገ-መንግስት ታሪክ ላይ ሰፋ ያለ ማብራሪያ የሰጡሲሆን፤ ከአጤ ሀይለስላሴ መንግስት ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የሆኑ ህገ-መንግስቶች በሂደታቸዉ ከላይ በስልጣንና በአጠቃላይ የፖለቲካል ልሂቃን ወደ ህዝቡ የተጫኑ መሆናቸዉን አብራርተዋል፡፡ምሁሩ እንዳሉት የሀገራችን ህገ-መንግስቶች በዚህ ምክንያት የህዝብ ፍላጎትን በተሟላ መልኩ ሳያንፀባርቁ ቆይተዋል፡፡
በ1987 ዓ.ም የፀደቀዉ የኢፌደሪ ህገ-መንግስትም በሂደቱ በተገቢዉ መንገድ ህዝብን ያላሳተፈና በወታደሪዊ ትግል ደርግን አሸንፈዉ ስልጣን የተቆናጠጡ ሀይሎች ከፍተኛ ተፅዕኖ ያረፈበት ሰነድ እንደሆነ ተደርጓል ብለዋል፡፡ዶ/ር ሲሳይ በማብራሪያቸዉ አክለዉም በስራ ላይ ያለዉ የአሁኑ ህገ-መንግስት ከአመጣጥ ሂደቱ ባለፈ ሰፊ የይዘትና የቅርፀ ችግር እንዳለበት ገልጠዋል፡፡
ምሁሩ እንዳሉት በአሁኑ የሀገራችን ፖለቲካ የኢፌዲሪ ህገ-መንግስትን በተመለከተ ሁለት አይነት ፅንፎች (extremes) አሉ፡፡አንደኛዉ ፅንፍ ህገ-መንግስቱ ምንም እንከን የሌለዉና አልፎም ሀገሪቷን የታደገ ነዉ የሚል ነዉ፡፡ሁለተኛዉ ደግሞ ህገ-መንግስቱ በአጠቃላይ በዉስብስብ ችግር የተሞላ ስለሆነ መቀየር አለበት የሚል ነዉ፡፡ ዶ/ር ሲሳይ እነዚህ ሁለት ፅንፎች ትክክል እንዳልሆኑና ሌላ ሦስተኛ አማራጭ እንዳለ ጠቁመዋል፡፡ይህም መሠረታዊ የህገ-መንግስት ክለሳ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የኢፌዲሪ ህገ-መንግስት ብዙ መሠረታዊ ጭብጦች የሀገራችን ፖለቲካ ቀዉስ መነሻ መሆናቸዉን የተለያዩ አንቀፆችን በመጥቀስ በስፋት አብራርተዋል፡፡ በመሆኑም ህገ-መንግስቱ እንደገና በስፋት ታይቶ መከለስ እንዳለበት ዶ/ር ሲሳይ መንግስቴገ ልፀዋል፡፡